ጰራቅሊጦስ(መንፈስ ቅዱስ)

†✝† እንኩዋን ለጥንተ በዓለ ጰራቅሊጦስ (መንፈስ ቅዱስ) በሰላም አደረሳችሁ †✝†



 #በዓለ_ጰራቅሊጦስ



የጌታችን ዓበይት በዓላቱ 2 ጊዜ (ማለትም ጥንተ በዓልና የቀመር በዓል ተብለው) ይከበራሉ:: ዛሬም ከ1,973 ዓመታት በፊት አምላካችን መንፈስ ቅዱስ በቅዱሳን ሐዋርያት ላይ መውረዱን እናስባለን::



††† ይህስ እንደ ምን ነው ቢሉ:-



+ቸር አምላክ ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛ ሲል

*ከልዑል ማዕርጉ ወርዶ:

*በማሕጸነ ድንግል ተጸንሶ:

*በኅቱም ድንግልና ተወልዶ:

*ከኃጢአት በቀር በግዕዘ ሕጻናት አድጐ:

*በ30 ዘመኑ ተጠምቆ:

*ቅድስት ሕግ ወንጌልን አስተምሮ:

*በፈቃዱ ሙቶ:

*በባሕርይ ስልጣኑ ተነስቶ:

*በአርባኛው ቀን ያርጋል::



+ታዲያ ደቀ መዛሙርቱን የቅዱስ መንፈሱን ጸጋ ተስፋ እንዲያደርጉ ነግሯቸው

ነበርና በተነሳ በ50ኛው ቀን: በዐረገ በ10 ቀን ተስፋውን ፈጸመላቸው::



+እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ዶሮ ጫጩቶቿን በክንፎቿ እንድትይዝ

በአንድ ላይ ሰብስባ ለክብረ መንፈስ ቅዱስ አብቅታቸዋለች:: 120ው ቤተሰብ

ከጌታችን እናት ጋር ሲጸልዩ መንፈስ ቅዱስ በአውሎ ንፋስ አርአያ ወርዶ

በአምሳለ እሳት አደረባቸው::



+ቅዱሳን ሐዋርያት ፈሪዎች የነበሩ ደፋሮች: አሮጌ ሕሊና የነበራቸው

ሐዲሶች ሆኑ:: በአዕምሮ ጐለመሱ: ቁዋንቁዋ ተናገሩ: ምሥጢርም

ተረጐሙ:: በቅጽበትም ብሉይ ከሐዲስ በልቡናቸው ውስጥ ተሞላ::



+ሐዋርያቱ ቅዱስ መንፈስን ተቀብለው ዓለምን በወንጌል ዕርፈ መስቀል

አርሰዋል:: አልጫውን ዓለም ጨው ሆነው አጣፍጠዋል:: ሳይሳሱም

አንገታቸውን ለሰይፍ ሰጥተዋል::

"ኪያሁ መንፈሰ ነሢኦሙ ለለአሐዱ:

ሐዋርያት ለሰቢክ አሕጉራተ ዓለም ዖዱ:

ሰማዕትኒ ለሕማም ነገዱ::" እንዳለ ደራሲ::



+በዚህ ቀን 2 ነገሮች በትኩረት ይነገራሉ:-

1."የመንፈስ ቅዱስ የባሕርይ አምላክነት:-"

*እርሱ ከአብ የሠረጸ: ቅድመ ዓለም የነበረ: በባሕርይ ስልጣኑ ከአብና

ከወልድ ጋር እኩል የሆነ: የራሱ ፍጹም አካል ያለው ፍጹም አምላካችን

ነውና::



2."ቅድስት ቤተ ክርስቲያን:-"

*አብ ያሰባት: ወልድ በደሙ የቀደሳት: መንፈስ ቅዱስ በጸጋው ያጸናት

የክርስቲያኖች አማናዊት አንድነት: አንድም ቤት ናትና:: ዛሬ በጉባዔ

ተመስርታለች::



=>+"+ በዓለ ሃምሳም የተባለው ቀን በደረሰ ጊዜ ሁሉም በአንድ ልብ ሆነው

አብረው ሳሉ ድንገት እንደሚነጥቅ አውሎ ነፋስ ከሰማይ ድምጽ መጣ::

ተቀምጠው የነበሩበትንም ቤት ሁሉ ሞላው:: እንደ እሳትም የተከፋፈሉ

ልሳኖች ታዩአቸው:: በእያንዳንዳቸውም ላይ ተቀመጡባቸው:: በሁሉም

መንፈስ ቅዱስ ሞላባቸው:: መንፈስም ይናገሩ ዘንድ እንደሰጣቸው በሌላ

ልሳኖች ይናገሩ ጀመር:: +"+ (ሐዋ. 2:1-4)



<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>

አስተያየቶች